Friday, 20 May 2016

የዋና ኦዲተር ሪፖርት የመንግሥት ተቋማት የፋይናንስ ጥሰትና አፈጻጸም ከዓመት ዓመት እየባሰበት ነው አለ

  • ከሁለት ቢሊዮን ብር በላይ ያልተወራረደ ሒሳብ ተገኝቷል
  • ጊዜው ያለፈባቸው አደገኛ ኬሚካሎች ለዜጎች እየተሸጡ ነው
  • ሊብሬ ያላቸው ተሽከርካሪዎች በአካል የት እንደገቡ አይታወቅም
  • የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣንና ዩኒቨርሲቲዎች ተወቀሱ
gemechuየፌዴራል ዋና ኦዲተር ጽሕፈት ቤት የፌዴራል መንግሥት መሥሪያ ቤቶች የ2007 የበጀት ዓመት ሒሳብ ኦዲት ማክሰኞ ግንቦት 9 ቀን 2008 ዓ.ም. ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በቀረበው ሪፖርት፣ አብዛኞቹ በጀት ተቀባይ የመንግሥት ተቋማት አስደንጋጭ የተባለ የሕግ ጥሰት የተገኘባቸው መሆኑን አስታወቀ፡፡ በዚህ ሪፖርት መነሻም ፓርላማው በአስፈጻሚ አካላት ላይ ቁጣውን ገልጿል፡፡
ዋና ኦዲተሩ አቶ ገመቹ ዱቢሶ በምክር ቤቱ ተገኝተው ባቀረቡት ሪፖርት፣ ብዛት ያላቸው የመንግሥት ተቋማት በተደጋጋሚ በየዓመቱ የሚሰጣቸውን አስተያየት ተግባራዊ በማድረግ ከማሻሻል ይልቅ፣ ወደባሰ ጥፋት እየገቡ መሆናቸውንና ለዚህም ዋና ምክንያቱ ተጠያቂ ያለመደረጋቸው መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ዋና ኦዲተር ጽሕፈት ቤት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በስተቀር በሁሉም መሥሪያ ቤቶች የኦዲት ሥራ ማከናወኑን አስታውቋል፡፡ ዋና ዋና የተባሉና ልዩ ትኩረት የሚሹ የኦዲት ግኝቶችን ዋና ኦዲተር ለምክር ቤቱ አቅርበዋል፡፡
ዋና ኦዲተሩ አቶ ገመቹ አጠቃላይ ሪፖርታቸው በመንግሥት መሥሪያ ቤቶች የፋይናንስና ሕጋዊነት ኦዲት፣ በክዋኔ ኦዲትና በመሠረታዊ አገልግሎቶች ከለላ ድጋፍ (PBS) ላይ ባተኮሩ ሦስት ክፍሎች የቀረበ ነበር፡፡
ምንም እንኳ ተጠያቂ መደረግ አለባቸው የተባሉ የተለያዩ ተቋማት በዝርዝር ሪፖርቱ የተካተቱ ቢሆንም፣ በኦዲት ግኝቱ ስማቸው የተነሳው የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣንና አሥር ያህል ዩኒቨርሲቲዎች ናቸው፡፡
በሕግ በተደነገገው መሠረት የሰነድ ሒሳብ በወቅቱ መወራረዱን ለማጣራት በተደረገው የኦዲት ሥራ፣ በ94 መሥሪያ ቤቶችና በ11 ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶች 2.079 ቢሊዮን ብር በደንቡ መሠረት በወቅቱ መወራረድ አለመቻሉን ሪፖርቱ ያሳያል፡፡
ከዚህ ውዝፍ ሒሳብ ውስጥ ከፍተኛውን ድርሻ የያዙት የመንግሥት ግዢና ንብረት ማስወገድ አገልግሎት፣ የትምህርት ሚኒስቴር፣ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፣ የአገር መከላከያ ሚኒስቴር፣ ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ፣ ወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡
በተሰብሳቢ ሒሳብ ላይ የታዩ ዋና ዋና የአሠራር ችግሮች ያሉትን አቶ ገመቹ በዝርዝር ያቀረቡ ሲሆን፣ በአራት መሥሪያ ቤቶች የተሰብሳቢ ሒሳብ ተቀፅላ ሌጀር ያልተዘጋጀላቸው ሒሳብ ከ174 ሚሊዮን ብር በላይ ተገኝቷል ብለዋል፡፡
በገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ሥር ባሉ ሦስት ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶችና በሌሎች ሁለት መሥሪያ ቤቶች ከ15.9 ሚሊዮን ብር በላይ በወጪ ተመዝግቦ ሪፖርት መደረግ ሲገባው፣ ያላግባብ በተሰብሳቢ ሒሳብ ተይዞ መገኘቱን አስረድተዋል፡፡
የመንግሥት ገቢ በወጡት ሕጎች መሠረት በአግባቡ መሰብሰቡን ለማጣራት በተደረገ ኦዲት፣ በ34 መሥሪያ ቤቶችና በገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ሥር ባሉ አሥራ አምስት ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶች በድምሩ 118.7 ሚሊዮን ብር፣ እንዲሁም በአንድ መሥሪያ ቤት ተማሪዎች በገቡት ውል መሠረት ግዴታቸውን ባለመወጣታቸው ያልተሰበሰበ 211,930 ዶላር ግብር፣ ቀረጥና ታክስ አለመሰብሰቡንም ጨምረው ገልጸዋል፡፡
በገቢ ሰብሳቢ መሥሪያ ቤቶችና ድርጅቶች ከፍተኛ የሚባሉ ገንዘቦች አለመሰብሰባቸውን የዋና ኦዲተር ሪፖርት በዝርዝር አስፍሯል፡፡ ለአብነትም በገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ከ689 ሚሊዮን ብር በላይ በበጀት ዓመቱ አለመሰብሰቡን አሳይቷል፡፡
የገቢ ሒሳብ ሪፖርት ውስጥ ያልተካተተ ገቢን አስመልክቶ የኦዲት ግኝቱ እንደሚያስረዳው፣ ገቢ እንዲሰበሰቡ በተፈቀደላቸው ተቋማት በትክክል ተመዝግቦ በገንዘብና ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስቴር መቅረቡን ለማረጋገጥ በተደረገ የኦዲት ሥራ በስድስት መሥሪያ ቤቶች ከ76.7 ሚሊዮን ብር በላይ፣ በሌሎች አምስት መሥሪያ ቤቶች በገንዘብ መጠን ያልተገለጸ የውስጥ ገቢ ባቀረቡት ዓመታዊ የገቢ ሒሳብ ሪፖርት ሳይካተት መገኘቱን አቶ ገመቹ ለምክር ቤቱ ገልጸዋል፡፡
የገቢ ሒሳብ በሪፖርት ከማያካትቱት መሥሪያ ቤቶች አብዛኞቹ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ሲሆኑ፣ ይህ አሠራር በገቢ ሒሳብ ላይ የሚደረገውን ቁጥጥር በማላላት ለምዝበራ በር የሚከፍት ከመሆኑም በላይ፣ መሥሪያ ቤቶቹ በራሳቸው የሚያዘጋጁዋቸው የሒሳብ መግለጫዎች የመንግሥት አጠቃላይ ገቢና ወጪ ሒሳብ ትክክለኛ ገጽታ እንዳያሳዩ ያደርጋል ብለዋል፡፡
በወጪ ሒሳብ አያያዝ፣ በግንባታ ኮንትራት ውል፣ በግዢና ንብረት አወጋገድና አስተዳደር ከፍተኛ የሕግ ጥሰትና አግባብነት የጎደለው አሠራር በአብዛኞቹ መሥሪያ ቤት ቢታዩም፣ ከፍተኛ ችግር የታየባቸውም ሆነ በተከታታይ ዓመታት መሻሻል ያላሳዩት አብዛኞቹ ዩኒቨርሲቲዎች መሆናቸውን ዋና ኦዲተሩ ገልጸዋል፡፡
የወጪ ሒሳብን በተመለከተ በ24 መሥሪያ ቤቶች የተሟላ መረጃ ሳይቀርብ ከ221.8 ሚሊዮን ብር በላይ በወጪ ተመዝግቦ መገኘቱን የኦዲት ሪፖርቱ ያመለክታል፡፡ የተሟላ የወጪ ማስረጃ ሳይቀርብ በወጪ ከመዘገቡት መሥሪያ ቤቶች ትምህርት ሚኒስቴር 95,526,864.83 ብር፣ ሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ 26,417,436.86 ብር፣ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ 10,000,000 ብር፣ አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ 8,601,445.18 ብር፣ ሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሲቲ 5,100,434.00 ብር፣ ወሎ ዩኒቨርሲቲ 4,646,850.00 ብር ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡
እንዲሁም ኦዲት በተደረጉ 56 መሥሪያ ቤቶችና አራት ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶች ከደንብና ከመመርያ ውጪ ያላግባብ 61,397,293.70 ብር ተከፍሎ መገኘቱን የዋናው ኦዲተሩ ሪፖርት ያመለክታል፡፡
ማንኛውም ግንባታ ሲከናወን ሥራው በትክክል ስለመሠራቱ ብቃቱ ተረጋጋጦ የማማከር አገልግሎት እንዲሰጥ በሚመለከተው መንግሥታዊ አካል ፈቃድ በተሰጠው አማካሪ ድርጅት ሲረጋገጥ ብቻ፣ ክፍያዎች ሊፈጽሙ እንደሚገባ የሕግ አግባቡን ዋና ኦዲተሩ አስረድተዋል፡፡ ሆኖም በአራት መሥሪያ ቤቶች የፕሮጀክቶችን ሥራ እንዲከታተሉ የተቋቋሙ፣ ነገር ግን የማማከር ፈቃድ በሌላቸው የግንባታ ጽሕፈት ቤቶች በኮንትራክተሮች የተሠራው ሥራ ትክክለኛነት እየተረጋገጠ በሐሮማያ ዩኒቨርሲቲ 717,312,735.03 ብር፣ በዲላ ዩኒቨርሲቲ 74,495,345.59 ብር፣ በሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ 35,419,596.22 ብር እና በአክሱም ዩኒቨርሲቲ 7,428,032.90 ብር በድምሩ 834,655,709.74 ብር ገንዘብ ወጪ ሆኖ ተገኝቷል ሲሉም ገልጸዋል፡፡
የእነዚህን ዩኒቨርሲቲዎች ጉዳይ በተመለከተ ተጠያቂ የማድረግ ዕርምጃ ከመውሰድ በተጨማሪ የመፍትሔ ሐሳብ ያሉትንም አቶ ገመቹ ለምክር ቤቱ አስረድተዋል፡፡ ዩኒቨርሲቲዎች ከዓመት ዓመት የሚፈጸሙት ስህተት እየተባባሰ በመሆኑ በትምህርት ላይ ብቻ እንዲያተኩሩ፣ ግዢ፣ ግንባታንና መሰል ሥራዎችን በተመለከተ ሌላ ተቋም ማቋቋም እንደሚገባ፣ ወይም በትምህርት ሚኒስቴር ሥር ለዚህ ዓላማ አንድ ዘርፍ እንዲቋቋም በማለት ለምክር ቤቱ አሳስበዋል፡፡ ነገር ግን ትምህርት ሚኒስቴር በራሱ ብዙ የኦዲት ችግር ከተገኘባቸው መሥሪያ ቤቶች አንዱ በመሆኑ፣ ይህንን ሥራ በአግባቡ ስለመፈጸሙ በአንዳንድ የምክር ቤቱ አባላት ጥያቄ ተነስቶበታል፡፡
በሌላ በኩል የምክር ቤቱን አባላት ያስደነገጠው ሌላው ጉዳይ በግብርና ምርት ማሳደጊያዎች አቅራቢ ድርጅት፣ የአገልግሎት ጊዜያቸው ያለፈባቸው ኬሚካሎች ለአርሶ አደሮች የሚሸጡ መሆናቸው በዋና ኦዲተሩ ሪፖርት ሲቀርብ ነው፡፡ የተለያዩ የመጠቀሚያ ጊዜያቸው ያለፈባቸው ኬሚካሎች በዝርዝር የተጠቀሱ ሲሆን፣ በኦዲት ሥራው ወቅት ኬሚካሎቹ ከሁለት ወራት እስከ ሁለት ዓመታት የመጠቀሚያ ጊዜያቸው ቢያልፍም በቀጥታ ለአርሶ አደሮች ሲሸጡ መታየታቸው በሪፖርቱ ተካቷል፡፡
በተጨማሪም በመድኃኒት ፈንድና አቅርቦት ኤጀንሲ የተገዙ ግምታቸው 570 ሚሊዮን ብር የሚሆኑ መድኃኒቶች፣ በዋናው መሥሪያ ቤትና በቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶች በመጋዘን ተቀምጠው የመጠቀሚያ ጊዜያቸው አልፎ መገኘቱንም አቶ ገመቹ ለምክር ቤቱ አስረድተዋል፡፡
ሕፃናትን በጉዲፈቻ መልክ ወደ ውጭ መላክን በተመለከተ የዋና ኦዲተር ሪፖርት ግኝቱንም አመላክቷል፡፡ በተለይ የሴቶችና ሕፃናት ሚኒስቴር የሚመለከታቸው ኃላፊዎች ከ2004 እስከ 2007 ዓ.ም. ባሉት ጊዜያት ውስጥ በናሙና ተመርጠው በታዩት የጉዲፈቻ አስፈጻሚ ድርጅቶች፣ ወደ አሜሪካና አውሮፓ ሕፃናትን በላኩባቸው አገሮች ጉብኝት ማድረጋቸው በሪፖርቱ ተመልክቷል፡፡ ነገር ግን ኃላፊዎቹ በሄዱባቸው አገሮች ያገኙዋቸው በጉዲፈቻ የተሰጡ ሕፃናት ደኅንነታቸው መጠበቁንና የጉዲፈቻ ተጠቃሚ መሆናቸውን የጉብኝት ዝርዝር ሪፖርት ቢያቀርቡም፣ እንዲሁም ባቀረቡት ሪፖርት መሠረት አስፈላጊውን ዕርምጃ መውሰድና ግብረ መልስ ሊሰጡ የሚገባ ቢሆንም ይህ የማይፈጸም መሆኑን በሪፖርቱ ተገልጿል፡፡
የገቢና ወጪ ዕቃዎችን በተመለከተ ወደ አገር ውስጥ እንዳይገቡ ወይም እንዳይወጡ በኢትዮጵያ ተስማሚነት ምዘና ድርጅት የላብራቶሪ ውጤት፣ ወይም ዓለም አቀፍ የሦስተኛ ወገን ሠርተፊኬት አምጥተው ትክክለኛነቱ ተረጋግጦ ደረጃቸውን የሚያሟሉ መሆናቸው ተረጋግጦ፣ ንግድ ሚኒስቴር ከሕግ አግባብ ውጪ በተቃራኒው ደብዳቤ በመጻፍ እንዲለቀቁ ማድረጉን የኦዲተሩ ሪፖርት አጋልጧል፡፡ እንዲሁም በሦስተኛ ወገን ሳይረጋገጡና የላቦራቶሪ ውጤት ሳይገለጽ ምርቶች ወደ አገር ውስጥ እንዲገቡ እያደረገ መሆኑንም ሪፖርቱ አመልክቷል፡፡
በንብረት አስተዳደርም በርካታ የኦዲት ግኝቶች ለምክር ቤቱ የቀረቡ ሲሆን፣ የፓርላማ አባላቱን በቁጭት ፈገግ ያሰኘው የኢትዮጵያ ብዝኃ ሕይወት ኢንስቲትዩት በስሙ ከተመዘገቡ ተሽከርካሪዎች ውስጥ አሥሩ ሊብሬ ቢኖራቸውም፣ ተሽከርካሪዎቹ የት እንደደረሱ ምንም የማይታወቅ መሆኑን አቶ ገመቹ ሲገልጹ ነው፡፡
ከዋና ኦዲተሩ ሪፖርት በኋላም የት እንዳሉ የማይታወቁትን አሥሩን የኢንስቲትዩቱ ተሽከርካሪዎች አስመልክተው አስተያየት የሰጡት የምክር ቤቱ አባል አቶ ዱቤ ጂሎ፣ ‹‹ባለፉት ቀናት ከ88 በላይ የኮንዶሚኒየም ሕንፃዎች ጠፉ ተባልን፡፡ ዛሬ ደግሞ አሥር ተሽከርካሪዎች ከአንድ ተቋም ከጠፉ ነገ የተገነባ መንገድ ጠፋ የማንባልበት ምክንያት ላይኖር ነው?›› በማለት አስተያየት ሰጥተዋል፡፡
በዕለቱ አስተያየትና ጥያቄዎችን ሲያቀርቡ የነበሩ አብዛኛዎቹ የምክር ቤት አባላት ዋና ኦዲተሩን አቶ ገመቹን ላቀረቡት ሪፖርት ውዳሴና አድናቆት ሲያቀርቡላቸው፣ በሌላ በኩል ደግሞ የሥራ አስፈጻሚውን አካል ሲተቹ ውለዋል፡፡
ወ/ሮ ሙሉ ገብረ እግዚአብሔር የተባሉ የምክር ቤት አባል በሪፖርቱ ማዘናቸውን ገልጸው እያንዳንዱ መሥሪያ ቤት በሕግ ሊጠየቅ ይገባዋል ካሉ በኋላ፣ ‹‹ከዚህ በኋላ አንላቀቅም፡፡ ከማንኛውም አካል ጋር እንጠያየቃለን፤›› ሲሉ ተናግረዋል፡፡ እኚሁ አባል፣ ‹‹ለብዙ ዓመታት የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ከተዘፈቀበት መውጣት አለመቻሉን ስመለከት ለእኔ ጥያቄ ብቻ ሳይሆን፣ እስከ መክሰስ የሚያደርስ ዕርምጃ መወሰድ አለበት፤›› ሲሉ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡
ዩኒቨርሲቲዎችንም በተለመከተ ሕግ፣ አካውንቲንግ ወይም ማንኛውንም የትምህርት ዓይነት የሚያስተምር ተቋም እንዴት የራሱን ስህተት ሊያርም አይችልም በማለት ጠይቀዋል፡፡
አቶ መሐሪ ዘለቀ የተባሉ ሌላ የምክር ቤት አባል በበኩላቸው፣ ‹‹ጊዜ ያለፈባቸውን ኬሚካሎች የሚሸጥ ተቋምን በአስተያየት ብቻ ማለፍ የለብንም፡፡ በሕግ ጭምር የግድ መጠየቅ አለበት፡፡ በሰው ሕይወት የራሱን ትርፍ ለማጋበስ የሚሞክር ተቋም ዝም ሊባል አይገባውም፤›› ብለዋል፡፡
በተደጋጋሚ ዓመታት ተመሳሳይ የኦዲት ግኝት ቀርቦባቸው መሻሻል በማያሳዩ ላይ በምክር ቤቱ በኩልም ሆነ በጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካይነት ዕርምጃ መወሰድ እንዳለበት፣ በርከት ያሉ የምክር ቤቱ አባላት ተመሳሳይ አቋማቸውን ሲሰነዝሩ ተስተውለዋል፡፡ ዋና ኦዲተሩ አቶ ገመቹ የመንግሥት ተቋማቱ በተደጋጋሚ የሕግ ጥሰት የሚፈጽሙት ተጠያቂ ባለመሆናቸው ምክንያት መሆኑን አስረግጠው ተናግረዋል፡፡
በምክር ቤቱ አሠራር መሠረት ለመጀመርያ ጊዜ ዋናው ኦዲተሩ ሪፖርታቸውን ሲያቀርቡ፣ የኦዲት ተደራጊ መሥሪያ ቤቶች ኃላፊዎች በምክር ቤቱ ተገኝተው ሪፖርቱን እንዲከታተሉ በአፈ ጉባዔው ጥሪ ተገኝተዋል፡፡ ነገር ግን ከሰዓት በኋላ በነበረው የጥያቄና መልስ ክፍለ ጊዜ አብዛኛዎቹ የተቋማቱ ኃላፊዎች ባለመገኘታቸው በአንዳንድ የምክር ቤቱ አባላት ትችት ተሰንዝሮባቸዋል፡፡By ሳተናው
ምንጭ – ሪፖርተር

የደም አበባ Blood Flower (አገሬ አዲስ)

blood flower“ የፍቅርና  የደስታ መግለጫ የሆነው አበባ በኢትዮጵያ ውስጥ የስቃይና የበሽታ ምክንያት  ሆኗል።” ዜምብላ የደች ቴሌቪዥን ፕሮግራም 18-05-2016
በአፍሪካ ውስጥ ከሚካሄደው ዓይን ያወጣ ዓለም አቀፍ ብዝበዛ ኢትዮጵያም አላመለጠችም።በላይቤሪያ፣በአይቮሪኮስት፣በኮንጎ፣በናይጀሪያና እንዲሁም በቀሩት የአፍሪካ አገሮች የአውሮፓውያን ኩባንያዎችና ባለጸጎች የሚካሄደው የማዕድን ብዝበዛው ጣራ ነክቶ፣ በባለጸጎቹ ቀስቃሽነት በአገር በቀሎቹ ተባባሪዎች መካከል በተነሳው የጥቅም ግጭት ምክንያት የብዙ ሕዝብ ህይወት ጠፍቷል።ለአገራቸው ጥቅምና ለሕዝባቸው መብት የተከራከሩት በዓለም አቀፍ የብዝበዛ ተቋማት ጥያቄና ትእዛዝ በአደባባይ ተረሽነዋል። እንደ ናይጀሪያ ባሉት አገሮችም በደችና በእንግሊዞች ንብረት በሆነው የሼል መልቲናሽናል የነዳጅ ኩባንያ ትእዛዝና ጥያቄ በስቅላት ተቀጥተዋል።በተለያዩት የአፍሪካ አገሮች እየተዘረፈ በሚወጣው ማዕድን ምክንያት በአገሮች የደረሰውን ቀውስና የጠፋውን የሰው ህይወት በሚመለከት በታዛቢዎች አጠራር ና ስያሜ የደም አልማዝ፣የደም ወርቅ፣የደም ዘይት(Blood Daimond,Blood Gold,Blood oil…)የሚል መጠሪያ ተሰጥቶታል።በኢትዮጵያም ውስጥ በከፍተኛ ደረጃ ከሚካሄዱት የዘረፋ ክንውኖች መካከል አንዱና ትልቁ የደቾች የአበባ እርሻ ነው።ይህም እንደሌሎቹ የ ደም አበባ ተብሎ ቢሰየም ትክክልና አግባብ አለው ብዬ አምናለሁ። ለዚህም ነው እርእሱን የመረጥኩት።
ከአስራ ሁለት ዓመት በፊት ማለትም በ2004 እ.አ.አ.የዛሬ አስራ ሁለት ዓመት ሸር/Share/በሚል ስም የተቋቋመው የአበባ እርሻ ኩባንያ ባለቤቱ ባርነሆልም/Baarnholm/ የተባለ ባለጸጋና ልጁ ናቸው፤ እናት ኩባንያው/Mother company/ አፍሪ ፍሎራ /Afri Flora/የተባለ ሲሆን አልስሚር/Aalsmeer/በተባለው የአበባ አምራችና አሰራጭ ማእከል (ሴንተር) አካባቢ የሚንቀሳቀስ ነው።
ይህ ኩባንያ በመጀመሪያ በ1997 እ.አ.አ.በኬንያ ውስጥ ተመሳሳይ የአበባ እርሻ ጀምሮ ከባቢውን ከበከለና ፣የውሃ ሃብቱን ካመከነ በዃላ የሥራው እንቅስቃሴ በመዳከሙ ንብረቱን በ50 ሚሊየን ኤሮ ሸጦ ፊቱን ወደ ኢትዮጵያ አዞረ።በመንግሥት ባለስልጣኖች ተባባሪነትና ሽርክና ብሎም የሙስና ሰንሰለት በዝዋይ ሃይቅ አካባቢ በ1000(አንድ ሽህ)የእግር ኳስ ሜዳ በሚሆን ሰፊ የእርሻ መስክ ላይ ስራውን ጀመረ።የከባቢውን የውሃ ሃብት እንደልቡ ካለምንም ቁጥጥር ለመጠቀም የከባቢውና የሃይቁ ባለቤት ለመሆን በቃ።
በመንግሥትና በኩባንያው ባለቤቶች የሚሰጠው መግለጫ ለከባቢው ልማትና ለነዋሪው የሥራ እድል የሚፈጥር እንደሆነ ተደርጎ ቢሆንም በተግባር ግን ሲታይ የዚያ ተጻራሪ ሆነ።በእርሻው መስክና በአበባው እንክብካቤ አስር ሽህ የሚሆኑ ሰራተኞች በተለይም ወጣቶች የተሰማሩ ሲሆን የሚከፈላቸው ደመወዝ ከዝቅተኛ መደብ ያነሰ ከመሆኑም በተጨማሪ ለእርሻው የተባይ መከላከያ ለሚረጨው መርዝ የተጋለጡና ለልዩ ልዩ በሽታ ሰለባ ሆነዋል።ይህን በሚመለከት ከአስር ዓመት በፊት “ትዝብት” በሚለው እርእስ  በተከታታይ አወጣው በነበረው ጽሁፍ የሚካሄደውን በደልና ሊያደርስ የሚችለውን የከባቢ አደጋ በማመልከት ላገርና ለወገን የሚቆረቆሩ እርምጃ እንዲወስዱ አሳስቤ ነበር።በኔዘርላንድ የሶሻሊስት ፓርቲም ባለኝ ግንኙነት ሁኔታውን አስረድቼ ጉዳዩ በይፋ እንዲወጣና የሰራተኛው ደመወዝ፣የጤና እንክብካቤና መከላከያ እንዲሟላ እንዲከታተሉ ጥያቄ አቅርቤ ነበር። በወቅቱ ይፋ ማድረጉ በስራው የተሰማራውን ደሃ  በዛን ጊዜ የሚያገኘውን በቀን ስምንት የኢትዮጵያ ብር እንዲያጣና  ለችግር ሊያጋልጥ ስለሚችል ኩባንያው ገና ሳይጠናከርና ለመውጣት በሚቀልበት ሁኔታ ጉዳዩን ከማንሳት ይልቅ ብዙ ወጭ ካደረገና ከተንሰራራ በዃላ መጠየቁ ይጠቅማል የሚል ውሳኔ ላይ ተደረሰ። በደች ኤምባሲ ዙሪያ በኢትዮጵያኑ ላይ የሚደርሰው መንገላታትና እንደውሻ በአገራቸው መጠለያ በሌለው በራፍ ላይ ለጠራራ  መጋለጣቸውን አስመልክቶ ላቀረብኩት አቤቱታ ከብዙ ውጣ ውረድ በዃላ ባለጉዳዩ በኤምባሲው ግቢ ውስጥ መጠለያ ክፍል ተሰርቶለት እንዲስተናገድ ለማድረግ ተችሏል።
በአበባው እርሻ ዙሪያ ግን ምንም ስር ነቀል መሻሻል ሳይታይ አንዳንድ የጥገና ለውጦች ተደረጉ ፤ከነዚያም ውስጥ የሰራተኛው ልጆች የሚማሩበት ትምህርት ቤትና የነጻ ህክምና አገልግሎት መቋቋማቸው ነው።ትምህርት ቤቱ ለከባቢው ኑዋሪ ልጆች የተከፈተ ሳይሆን ለሰራተኞቹ ልጆች ብቻ ነው፤ወላጆቻቸው ከኩባንያው ቢለቁ ወይም ቢባረሩ ልጆቹም ከትምህርት ቤቱ ይባረራሉ።የጤና አገልግሎቱም የተሟላ አይደለም።በሚረጨው መርዝ ሰውነታቸው የተጎዳው ሠራተኞች የህክምና እርዳታ ሲጠይቁ እርካሽና ቀላል መድሃኒት ተሰጥቷቸው ግፋ ቢል ከሶስት ቀናት እረፍት በዃላ ተመልሰው በዛው መርዘኛ ስራ ላይ እንዲሰማሩ ይገደዳሉ።ካሳና ድጎማ የሚባል ነገር አይታወቅም፤ለሕዝቡም፣ ለሠራተኛውም ታምርና ባዳ ነገር ነው።
ከጧቱ አንድ ሰዓት እስከ ምሽቱ አራት ሰዓት በቀን ከአስራ አራት ሰዓት በላይ በሳምንት ስድስት ቀን ለሚደክሙበት ሥራ የሚከፈላቸው ደመወዝ በጣም የሚዘገንን ነው።በወር 700 የኢትዮጵያ ብር በኢሮ ሲሰላ € 29.00 ብቻ ነው። በደች ገበያ የአንድ ዘለላ ጽጌሬዳ ዋጋ አንድ ኤሮ ተኩል ማለትም ከ35 የኢትዮጵያ ብር በላይ እንደሆነ ከግንዛቤ ውስጥ አስገብተን ከሰራተኛው የቀን ደመወዝ ጋር ሲነጻጸር የአንድ ዘለላ ጽጌሬዳ ሽያጭ ከፍተኛ እንሆነ እንረዳለን። ለአሁኑ የኑሮ ወጭ የሚበቃ አይደለም።አነሰ ሲሉ ተቀነሰ ነውና ከዚህም ላይ ግብር ተከፍሎበት በሰራተኛው እጅ ላይ በወር የሚገባው 650 የኢትዮጵያ ብር ይሆናል፡፤ለቤት ኪራይ ከአራት መቶ ብር በላይ ሲወጣ በቀሪው ገንዘብ በልቶና ጠጥቶ ለብሶ ለመኖር አለመቻሉን በቪዲዮው ላይ የተቀረጸውን ብሶት ማዳማጡ በቂ ነው።በጣም የሚገርመው ደግሞ ለአስር ሽህ  ኢትዮጵያውያን ሰራተኞች የሚከፈለው ደመወዝ 290.000 ሆኖ ሳለ ለ42 የደች ዜጎች የሚከፈለው ከሁለት ሚሊየን ኤሮ በላይ መሆኑ ነው።
የዚህን አይነት ሕገወጥ ተግባር በየአገሩ የሚፈጽሙ ድርጅቶች የሚያጭበረብሩበት መንገድ ፌር ትሬድ(fair trade) የሚል ሰሌዳ በመለጠፍ ነው። ይህ የአበባ እርሻ ተቋም በዓለም አቀፍ የንግድ ሕግ መሰረት የተደነገገውን የዚህን የመልካም የንግድ አሰራር መመዘኛ የተከተለ አለመሆኑን ስለ ሰራተኛ መብት የሚከራከሩ የዓለም አቀፍ ድርጅቶች የሰራተኛውን ደመወዝ፣የስራውን ሁኔታ(salary and working conditions)በመከታተል የተሰጠው ስያሜ ትክክለኛና ተገቢ አለመሆኑን አረጋግጠዋል። እርሻው በከባቢ፣ በሕዝቡ ጤናና ኑሮ ላይ ያመጣውን አደጋ በሚመለከት እንደሚከተለው ቀርቧል፡፤አንድ ዘለላ ጽጌሬዳ ለማምረት ከአምስት እስከ አስር ሊትር ውሃ ፣ለአንድ ሄክታር የአበባ እርሻ ስድስት የኦሎምፒክ የዋና ገንዳ ውሃ፣ በየቀኑ እየተመረተ ወደ ሆላንድ ለገበያ ለሚቀረበው ሶስት ሚሊዮን ተኩል(3.5 ሚሊየን)፣በዓመት ደግሞ 1.5 ቢሊዬን ጽጌሬዳ ምርት በሄክታር 2000 የኦሎምፒክ የዋና ገንዳ ውሃ በዓመት እንደሚያስፈልግና ይህም ከዝዋይ ሃይቅ እየተሳበ/እየተመጠጠ እንደሚውል ባለሙያዎቹ  ባደረጉት ክትትልና ጥናት አረጋግጠዋል።የሃይቁ መጠን እየቀነሰ ከመምጣቱም በላይ በከባቢው የሚኖረው ሕዝብ ከሃይቁ የሚያገኘው ጥቅም በተለይም በአሳ ምርቱ ላይ ያደረሰውን ተጽእኖና ብከላ ብሎም ተመጋቢው የደረሰበት በሽታ ለአበባው መከላከያ ከሚረጨው መርዝ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት እንዳለው ጉዳዩን ይፋ ያደረጉት  የዜምብላ ፕሮግራም አዘጋጅ የሆኑት የደች ጋዤጠኞችና በከባቢው ያሉ የሕክምና ባለሙያዎች አጋልጠዋል።የጽንስ ማስወረድና ከዚህ በፊት የማይታወቁ በሽታዎች መከሰታቸውን ሃኪሙ አልደበቁም።የሃይቁ የውሃ መጠን እየቀነሰ በመምጣቱም የመሬት ውስጥ ውሃ ለመሳብ ጉድጓድ በመቆፈር ላይ እንዳሉ የሚያሳየው ስእላዊ ማስረጃ በመታገዱና በመከልከሉ የተሟላም ባይሆን በጥቂቱ  በሪፖርቱ ውስጥ ቀርቧል።የሃይቁና የመሬት ውስጥ ውሃው ሲነጥፍ  በኬንያ እንዳደረጉትና እንደለመዱት ለሕዝቡ የዘላለም በሽታና ለከባቢው ውድመት ዳርገው ጓዛቸውን ጠቅለው መውጣታቸው አይቀሬ ነው። ቀደም ሲል በሃረር ከተማ ዓለም ማያ ሃይቅ ላይ በጫት እርሻ ምክንያት የደረሰው ጥፋት ውድመት ሊታወሰን ይገባል።
ዜምብላ የተሰኘው ፕሮግራም በየአገሩ የሚካሄዱትን ተንኮሎችና ዘረፋዎች የሚያጋልጥ ሲሆን ከዚህም ቀደም ሲል H₰M የተባለው የስዊድን የልብስና ሞድ ኩባንያ በርካሽ የሰራተኛ ደመወዝና ወጭ ምክንያት ከባንግላዴሽ ወደ ኢትዮጵያ መግባቱን እንዳጋለጠ በጊዜው ለኢትዮጵያውያን ማሳወቄ የሚታወስ ነው። የቻይናዎችም የጫማ ፋብሪካ ባልታደለው የኢትዮጵያ ወጣት ላይ የሚያካሂደውን ኢሰብአዊ ተግባርና ዘረፋ በወቅቱ ያስተላለፈውን ማጋለጥና መረጃ ኢትዮጵያኑ እንዲያውቁት አድርጌአለሁ፤አሁንም የዚህ መልእክት ዓላማ እንደኔና በኔዘርላንድ ውስጥ ተቀምጠው በቴሌቪዥን የቀረበውን ዝርዝር ለመመልከት ያልቻሉትን በሌላ አገር የሚኖሩ ኢትዮጵያን እንዲረዱት  ሲሆን ሰምተው እንዲቀመጡ ሳይሆን ተገቢውን የመከላከል እርምጃ ተባብረው እንዲወስዱም ለማሳሰብ ነው።እንዳለፉት ጊዜያቶች ሰምቶ መቀመጡ ለወንጀለኞቹ ድጋፍና ማበረታቻ ከመሆን ሌላ በወገናችንና በአገራችን  ላይ የሚደርሰውን ጥቃት ወዶ መቀበል ይሆናል።በኢትዮጵያ ውስጥ የሚንቀሳቀሱት የውጭ አገርና የአገር ውስጥ የንግድ ተቋማት ለሰራተኛው ብቻ ሳይሆን ለአገሪቱ መክፈል የሚገባቸውን ግብርና ታክስ አይከፍሉም።ለማንኛውም ዝርዝሩን ከዚህ በታች ካለው የቪዲዮ ቅጅ ለመረዳት ይቻላል። በጣም የሚያሳዝነው በሆላንድ ውስጥ ይኖር የነበረውና ከጎሹ ወልዴ ጋር “መድህን”የተባለውን የፖለቲካ ፓርቲ የመሰረተው ዶር.ፍስሃ ጽዮን መንግስቱ ለተጠየቀው ጥያቄ ቀጥተኛ መልስ በመስጠት ፈንታ የሃብታምና የደሃው ልዩነት ማደጉን ብቻ መግለጹ የሚያስተዛዝብ ሆኖ አገኝቸዋለሁ።ከሙስና ጋር የተቆራኘው የስርዓቱና የመንግሥቱ መመሪያ መሆኑ ሲታወቅ ያንን ለማለት አለመፍቀዱና አለመድፈሩን ሕዝብ የሚያውቀውን መልስ አድርጎ ማቅረቡን በፕሮግራሙ ውስጥ ልትገነዘቡት ትችላላችሁ።ይህ የግብርና ታክስ ምሁር የተለያዩ ኩባንያዎች  በተለይም ይህ የአበባ አምራች ኩባንያ ለአገሪቱ መክፈል የሚገባውን ግብር አለማሟላቱን በድፍረት መግለጽ ሲገባው መሸፋፈኑ የምሁር ስነምግባሩን ከጥያቄ ውስጥ ጨምሮታል።
አብዛኛዎቹ  በተቃዋሚው ጎራ የሚገኙት የከባቢና የጎሳ ድርጅት መሪዎች የውጭ አገር ዘራፊዎችን የሚቃወሙት የጥቅም ተካፋይ ባለመሆናቸው እንጂ  ስልጣን ይዘው ለዚህ ዕድል ቢበቁ ከወያኔ የልተለዬ መመሪያ ይከተላሉ ብዬ አላምንም። አሁንም በአውሮፓ፣በአሜሪካና በካናዳ እየተዘዋወሩ የውጭ ባለሃብቶች ገብተው እንዲዘርፉ ቅስቀሳና ጥሪ የሚያደረጉት የአማራ ክልል ባለስልጣኖች የዚሁ ተባብረህ ዘርፈህ ጥፋ ዓላማ አካል ነው።By ሳተናው
ሙሉውን የዜምብላ ቅጅ ከዚህ በታች ባለው ሊንክ መከታተል ይቻላል፣
ሰምቶ እየተበሳጩ ከመቀመጥ ተባብሮ ችግሩን ማሶገድ ይሻላል
አገሬ አዲስ