.ነገስታቶቻችንን ከአማራነት መነጠል ምን ጉዳት ያመጣል?
******************************************************************
******************************************************************
አንድ የአማራ “ተቆርቋሪ” ሰው በተደጋጋሚ አጼ ቴዎድሮስ “ቅማንት” ናቸው ብሎ ይናገራል፤ ኧረ እንዲያውም ይህንኑ ኑፋቁ በጥራዝ መልኩ ጸፎአል አሉ፡፡ ታዲያ አንዲት አማራ ትበሳጭና እስኪ ማስረጃ ትለዋለች፡ እርሱም እግዜርን ሳይፈራ ሰውንም ሳያፍር “የታንጉት ምስጢር” ላይ ነው ያነበብኩት ይላል፡፡ ይህ ሰው አጼ ቴዎድሮስን ቅማንት ለማድረግ የታንጉት ምስጢርን ምስክር መጥራቱ ብቻ አይደለም ችግሩ፡፡ ትልቁ ችግር ይህንን መጽሀፍ አለማንበቡ ነው፡፡ ሶስተኛው ችግር ደግሞ አጼ ቴዎድሮስን ቅማንት ናቸው ሲል አማራን እና ቅማንት አማራን አራርቆ ለማስቀመጥ መሞከሩ ነው፡፡ (በነገራችን ላይ አጼ ቴዎድሮስ ቅማንት ናቸው የሚለው በራሱ ችግር አልነበረውም፡፡ ችግሩ ያለው በውስጡ ካዘለው ጸረ አማራ ፖለቲካዊ አጀንዳ ላይ ነው፡፡ እንጅማ ቅማንት አማራም ሆነ አማራ ያው አማራ ነው፡፡) ሌላኛው ችግር ደግሞ ለኢትዮጵያ ሲባል የአማራን ታሪክ ለማይፈልጉት ሁሉ መወርወር እና አማራን ታሪክ አልባ አድርጎ የማስቀረቱ ዘመን ያስቆጠረ ልማድ ቀጣይ ክፍል አራማጅ መሆኑ ነው፡፡ እግዜር ያሳያችሁ! ሌሎች ብሄሮችን ታሪክ እንዲሰሩ እና ከአማራ ጋር እንዲስተካከሉ ማድረግ ሲገባ የአማራን ዘርፎ አማራን ባዶ አድርጎ እነዛን ያልሰሩቱኑ ባለታሪክ ማድረግ! ይህንን የሚገልጽ አንድ ሌላ አማራዊ ገጠመኝ፡፡ በ1996 ዓ.ም. አማራ ከ8ኛ ክፍል በኋላ መማር የለበትም ተብሎ ፖሊሲ ወጥቶ ነበር፡፡ እስከ 8ኛ ክፍል ይማራሉ፤ ከዛ ወዲያ የራሳቸው ጉዳይ፡፡ ኦቦ አዲሱ ለገሰ ለምን እንዲህ ይደረጋል ተብሎ ተጠይቆ ሲመልስ “አማራ ከዚህ በፊት ስለተማረ ከሌሎች ጋር ለማስተካከል ነው” አይነት ንግግር ተናገረ፡፡ ገራሚ፡፡ ሌሎችን በማስተማር ከአማራ ጋር ማስተካከል ነው ወይስ አማራውን እንዳይማር ማድረግ ነው የሚገባው? ግን ቅንጅት መጥቶ የአማራን ወጣት ከዛ መከራ አተረፈው፡፡ ቅንጅት ለአማራ የዋለው ውለታ በዚህ ረገድ የሚረሳ አይደለም መቸም፡፡
ወደጥንተ ነገራችን እንመለስ፡፡ አንድ የብርሀኑ ዘርይሁን ጓደኛ የነበረ ሰው ብርሀኑ የታንጉት ምስጢርን እንዴት እንደጻፈው አጫውቶኝ ነበር፡፡ ብርሀኑ የታንጉት ምስጢርን ሲጽፍ የአዲስ ዘመን ስራ አስኪያጅ ነበር አለ፡፡ አንድ ጠረጴዛ ላይ በአንድ እጁ የታንጉት ምስጢርን ሲከትብ፤ በሌላ ወገን ተስተናጋጅ እና የስራ ባልደረቦች ስራ ሲሰጡት ደብተሩን እያጠፈ፤ እንደገና ስራና ሰው ቀለል ሲልለት ገልጦ እየጻፈ፤ እንደገና እየተዋከበ ነው የጻፈው አለ፡፡ ይህ ጓደኛየ ለብርሀኑ ዘሪሁን ያለውን አድናቆት ተናግሮ አይጠግብም፡፡ ብርሀኑ የታንጉት ምስጢርን በጻፈበት ውክቢያ ሁኔታ አይደለም መጽሀፍ የጋዜጣ አምድ ማዘጋጀት ፈታኝ እንደሆነ በተደጋጋሚ ይናገራል፡፡ ለዚህ ጓደኛየ ብርሀኑ በቃ ብርቱ ሰው ነው፡፡ እና በዛ ወከባ ውስጥ ሆኖ የጻፈው መጽሀፍ እስከዛሬም ድንቅ ነው፡፡
ያው እንግዲህ መጽሀፉ ታሪካዊ ልቦለድ ነው፡፡ ታሪካዊ ልቦለድ በመሰረታዊ ጭብጥነት ታሪክ እና አፈ ታሪክ ላይ የሚመረኮዝ ቢሆንም በደራሲው ምናባዊ ተጽእኖ ስር ስለሚወድቅ ለታሪክ ማጣቀሻነት አይውልም፡፡ እንዲህ አይነቱ ድርሰት ደራሲው ተጨባጭ ታሪኮችን እና አፈ ታሪኮችን ልብ አንጠልጣይ በሆነ ሁኔታ የሚጽፍበት እንጅ የታሪክ ሰነድ አገላብጦ ማጣቀሻ አስቀምጦ እውነትን ብቻ የሚያስቀምጥበት አይደለም፡፡
ያም ሆኖ የታንጉት ምስጢር ውስጥ ላይ አጼ ቴዎድሮስ ቅማንት ናቸው የሚል አይገኝም፡፡ መጽሀፉ ራሱ የታንጉት ምስጢር የተባለበት ምክንያት የአጼ ቴዎድሮስ አባት ታንጉትን ከቅማንት አማራ መውለዳቸው እና በኋላም ይህችን ታንጉትን ወንድምዋ አጼ ቴዎድሮስ ለታማኛቸው ፊታውራሪ ገብርየ ሚስት አድርገው ማጋባታቸው እና በጋብቻውም ፍሬ ማፍራት ባለመቻላቸው አሁንም ቅድምም “ኧረ ባባጃሌው” የምትለዋ ወፍራም ሴትዮ (ስሟን ረስቸዋለሁ) ታንጉትን በመጀመሪያ ጭልጋ ወይኒ ኪዳነምህረት ጸበል መውሰድዋ (ይህ የወይኒ ኪዳነ ምህረቱ የጸበል ጉዳይ በአቤ ጉበኛ “አንድ ለእናቱ” መፅሀፍ ላይም በስፋት መገለጹ ይታወሳል)፤ በጸበል አልሳካ ሲል አምባ ጊዮርጊስ በሚስጢር ከአንድ የቆሎ ተማሪ ጋር እንድትተኛ ተደርጎ መጸነሱዋን እና ያንንም ወፍራሟ ሴት እና ታንጉት የገብርየ ልጅ ነው ብለው የማሳመናቸውንና የመሳሰለውን ውስብስብ የመንግስት ፖለቲካ ለማስረዳት ነው፡፡ የአጼ ቴዎድሮስ እህት ታንጉት በአንድ ወገን ከቅማንት አማራ ትወለዳለች፡፡ ነገር ግን አጼ ቴዎድሮስ እህቱ ቅማንት አማራ በመሆኑዋ ብቻ ቅማንት ነው ብለው የሚከራከሩ የአማራ “ተቆርቋሪዎች” ስናገኝ ያለንበት ዘመን እውነትም 8ኛው ሽህ መሆኑን በደምብ እንገነዘባለን፡፡ እዚሁ መጽሀፍ ላይ ፊታውራሪ ገልሞ የሚባል በጣም ጀግና ቅማንት አማራ ነበር፡፡ አጼ ቴዎድሮስ ይህንን ጀግና ሰው “ምነው ሁሉም ቅማንት እንዳንተ በሆነልኝ” እያሉ ያንቆለጳጵሱት እንደነበር ብርሀኑ ጸፎአል፡፡ የማንቆለጳጰሱ ነገር የደራሲው ምናብ ይሁን እውነታ ወደጎን እንተወው እና ፊታውራሪ ገልሞ የሚባል በጣም ጀግና ቅማንት አማራ ከአጼ ቴዎድሮስ ጎን ከእነ ራስ እንግዳ እና ፊታውራሪ ገብርየ ጋር ተሰልፎ እንደነበረ ግን በታሪክ የሚታወቅ ነው፡፡ (በነገራችን ላይ እስካሁን ድረስ አንድም አማራ ራሱን በፌስቡክ ራስ እንግዳ ብሎ በማስታወሻነት አለመሰየሙ አሳዝኖኛል)፡፡ አጼ ቴዎድሮስን ሀበሻ በሙሉ ከድቶ ከንጉሱ ጎን እስከመጨረሻው በታማኝነት ከቆሙት 5000 ወታደሮች አንዱ እና በጦርነቱም ለሚወደው ንጉስ እና ለቆመለት አላማ የተሰዋ ጀግና ነውና…. ራስ እንግዳ፡፡ ባጭር አገላለጽ ቅማንት አማራ የተበታተነውን አማራ ለማሰባሰብ በተደረገው እልህ አስጨራሽ የጀግንነት ስራ ከአጼ ቴዎድሮስ ጎን ሆኖ በህዝብ ሰብሳቢነት እና አገር አንድ አድራጊነት ጉልህ ሚና ተጫውቷል፡፡
እንግዲህ አማራ ላለፈው ግማሽ ክፍለዘመን DeAmharization Process ውስጥ ያለ ህዝብ ነው፡፡ አማራን በዚህ ኢ-አማራ ማድረግ ሂደት ውስጥ የተሳተፉት በሚያሳዝን ሁኔታ አማራ ያልሆኑቱ ብቻ አይደሉም፡፡ አማሮቹ ራሳቸው በስፋት ተሳትፈውበታል፤ አሁንም እየተሳተፉበት ነው፡፡ ኢትዮጵያዊያንን በስሜትም በግብርም እንደ አንድ ሰው አሳቢ እንደ አንድ ልብ መካሪ ለማድረግ የእያንዳንዱን ብሄራዊ ማንነት ማጥፋት መልካም ሊመስል ወይም ሊሆን ይችላል፡፡ ደራሲ ስብሐት ገብረ እግዚአብሔር ለጋዜጠኛ ዘነበ ወላ እንዳለው ፈረንሳዮች ኦምሌት ለመስራት እነቁላሉን መስበር ያስፈልጋል ይላሉ፤ አጼ ምኒልክም ኢትዮጵያን ለመፍጠር ወይም ኦምሌት ለመስራት እንቁላሉን መስበር ነበረባቸው፤ አጼ ምኒልክ እንቁላሉን ባይሰብሩት እና አማርኛን ባይሰጡን ኖሮ አንተ ከጋሞ እኔ ከትግራይ በምን እንግባባ ነበር ብለውት!
በሚያሳዝን ሁኔታ ግን ኢትዮጵያን ለመፍጠር ሁሉም እንቁላሎች ተሰብረዋል ማለት አይቻልም፡፡ ሌሎች እንቁላሎች እንዳሉ ሆነው አማራ ብቻ ተሰብሮ በስብርባሪው ሌሎችን እንቁላሎች እንዲያጣብቅ ነው የተደረገው፡፡ አማራ ተሰብሮ ሌላው ሳይሰበር የተሰራውም ኦምሌት ዛሬ የሌሎች አለመሰበር ህልውና እየተላወሰ እያየን ነው፡፡ የእነሱ ህልውናም አማራውን ጨርሶ ለማጥፋት ደርሷል፡፡ አሁን የተያያዝነው ሌሎችን እስከህይወታቸው ለማቆየት የተሰበረውን እንቁላል፤ አማራን፤ እንደገና መጠገን እና በብዙ ድካም ወደነበረበት መመለስ ነው፡፡ ኢትዮጵያን እንደ አገር እንደገና ለማቆም አማራ ብዙ ጊዜ ሲጨፈለቅ እና ሲሰባበር ነው የቆየው፡፡ በኋላም አማራ ማንነቱን ረስቶ ለኢትዮጵያዊነት ሲለውጥ ሌሎች ግን ስላልተሰባበሩ በነበሩበት ቆዩ፡፡ ስለዚህ የኢትዮጵያዊነት ፕሮጀክት ሲጀመርም ሁሉንም ማንነቱን አሳጥቶ አንድ የማድረግ ሂደትን ያልተከተለ ነበር፡፡ ውጤቱንም አሁን እያየነው ነው፡፡ ያለፉት መሪዎቻችን፤ ልሂቃን እና አሁን ያለው ልሂቅ አማራን ብቻ ማጥፋት ኢትዮጵያን ይገነባል ወይም አጣብቆ ያቆያል ብለው ያስባሉ፡፡ በጣም ስህተት፡፡ ይህ ግን በአማራ ሞት ላይ ለሌሎች ያልተሰበሩ እንቁላሎች ህይወት መስጠት ነው፡፡ አማራ እየተሰባበረ ሌላው ግን ሲፈለፈል ቆይቷል፡፡ ስለሆነም አንዲት ኢትዮጵያን ለመፍጠር የተደረገው ሂደት እና አሁንም እየቀጠለ ያለው ጥረት በአማራ ኪሳራ ላይ የተመሰረተ በመሆኑ ተቀባይነት የለውም፡፡ ለአማራ ጎጅ ነው፡፡ አማራ ብቻውን ለምን ይሰበር!?
ስለዚህ ሚዛናዊ ባልሆነው እንቁላል ሰበራ የተዳከመውን የአማራነት ስሜት ለማጠናከር እየጣርን ባለንበት በአሁኑ ሰአት የተዘረፈብን እና እየተዘረፍብን ያለውን ታሪክ አለምንም መታለል እና መዘናጋት ማስመለስ ወይም መመለስ አለብን፡፡ አማራነታችን ለሌሎች የመስዋእት በግ ሆኖ በነጻ እንደታደለው ሁሉ የአማራ የሆነው ነገር ሁሉ እንዲሁ በገፍ ተዘርፏል፡፡ ከላይ የኦቦ አዲሱ ለገሰ ምሳሌነት እንደሚያስረዳው አይነት ነገር ነው አማራ እና አማራነት እንዲሁም የአማራ የሆነው ሁሉ ላይ እየተካሄደ ያለው፡፡ በጣም በሚያናድድ መልኩ እኛም ራሳችን ሳናውቅ ወይም በግብዝነት ይህንን የአማራ የሆነውን ሁሉ ፍቆ የማጥፋት እና ለሌሎች የመሸለሙ ስራ ላይ በአጋዥነት ስንሰራ እንታያለን፡፡
ከላይ በአጼ ቴዎድሮስ ላይ የቀረበው የታንጉት ምስጢር አይነት ምስክር በአጼ ምኒልክና በአጼ ኃይለ ሥላሴ ላይ በስፋት ሲንጸባረቅ ይታያል፡፡ ለምሳሌ በመግቢያየ የጠቀስኩት የአማራ “ተቆርቋሪ” አጼ ምኒልክን እና አጼ ኃይለ ሥላሴን ከአማራነት ፍቆ ለሌላ አስረክቧል፡፡ ያው ማስረጃው መሰለኝና ደሳለኝ ቢሆንም ቅሉ! ማን ይሰማዋል! በተመሳሳይ እዚሁ ፌስቡክ ላይ በአማራ ብሄረተኝነት አምናለሁ የሚል ራሱን ካይማር ሠርፀ ድንግል ብሎ የሚጠራ ሰው አጼ ኃይለ ሥላሴን አማራ አይደሉም ብሏል፡፡ በጣም የሚገርመው ይህ ሰው ጉራጌን አማራ ነው ብሎ ያምናል፡፡ በዚህ ሰው አባባል ለምሳሌ በቅርቡ ብርጋዴር ጀኔራል ተስፋየ ሀብተማርያም ጉራጌ አማራ ሲሆን ከወሎ የተወለደውን የሻእብያና ኦነግ መጠቀሚያ የነበረውን ዋለልኝ መኮንንን በበረራ ልዩ ሀይልነቱ መግደሉን አወድሶ ጽፎአል፡፡ ነገር ግን አጼ ሀይለስላሴ አማራ አይደሉም የሚባልበት ምክንያት አንዱ ጉራጌ ደም አላቸው የሚለው ነው፡፡ ጉራጌን አማራ ያለ ሰው ታዲያ ከጉራጌ እና አማራ ተወለደ የተባለን ንጉስ እንዴት ብሎ ነው አማራ አይደለም የሚለው!!!!? በነገራችን ላይ አጼ ኃይለ ሥላሴ የጉራጌ ደም አላቸው የሚለውን በቂ ማስረጃ የለኝም፡፡ እንደማስረጃ የምጠቅሰው የታጋይ አንዳርጋቸው ጽጌን “ነጻነትን የማያውቁ ነጻ አውጭዎች”ን ነው፡፡ ታጋይ አንዳርጋቸው እዛ ላይ ቃል በቃል “በአጼ ምኒልክና አጼ ኃይለ ሥላሴ የደም ቧንቧ ከሚፈሰው የአማራ ደም ይልቅ የኦሮሞና ጉራጌ ደም ይበልጣል” ብሏል፡፡ ከየት እንዳገኘው አላውቅም፡፡ ይሁንና ይህም አባባል የተጠቀሰው ኢ-አማራ የማድረጉ ሂደት (DeAmharization Process) አንዱ አካል ነው፡፡
እንግዲህ ጉራጌ፤ ሀድያ፤ ከምባታና አደሬ በኦሮሞ ወረራ ከጥፋት ከተረፉት የጥንት የአማራ ክፍሎች የሚጠቀሱ መሆናቸው አያከራክርም፡፡ አጼ ምኒልክም ሆኑ አጼ ሀይለ ሥላሴ የጉራጌ ደም ቢኖራቸው አማራነታቸው እንደተጠበቀ ነው፡፡ እንደዋዛ መታለፍ የሌለበት ግን እነዚህ ነገስታት የኦሮሞ ደም አላቸው የሚለው የክህደት ነገር ነው፡፡ አጼ ምኒልክ የኦሮሞ ደም አላቸው የሚለው ነጭ ውሸት ነው፡፡ የዘር ሀረጋቸውን የንጉሱ ጸሀፌ ትእዛዝ ገብረ ሥላሴ “ታሪከ ዘመን ዘ ዳግማዊ ምኒልክ” በተሰኘው መጽሀፋቸው በተገቢው ዘርዝረው ጽፈውታል፡፡ እዛ ላይ መመልከት ነው፡፡ አጼ ኃይለ ሥላሴ ኦሮሞ ደም አላቸው የሚለው በጥልቀት መታየት አለበት፡፡ እንደሚባለው በአያታቸው ከሀረር ኦሮሞ ይወለዳሉ ነው፡፡ መልካም፡፡ ነገር ግን ኦሮሞ በሁለት ይከፈላል፡፡ ኦሮምኛ ተናጋሪ አማራ እና ኦሮሞ ተብሎ (ቢያንስ ከዚህ ጽሁፍ አንጻር)፡፡ እንደሚታወቀው የሀረር ኦሮሞ ኦሮምኛን ለረዥም ጊዜ በመናገሩ ወደኦሮሞነት የተቀየረ የጥንት አማራ ነው፡፡ ይህንን መሰል ጉዳይ የጀነቲክስ (ዘረመል) ጥናቶች እያፍታቱት ነው፡፡ ለወደፊቱም ኦሮምኛ በመናገር ብቻ ኦሮሞ መስሎት የሚኖረውን የጥንት አማራ ወገናችንን በዚህ መሰል ሳይንሳዊ ዘዴ ነው ወደቀደመ አማራ ማንነቱ የምንሰበስበው፡፡ ይህም ማለት አጼ ኃይለ ሥላሴ በአያታቸው ኦሮሞ ናቸው ቢባል እንኳ በዚህ መንገድ ኦሮምኛ በመናገር ላይ ከሚገኝ ከጥንት አማራ የተወለዱ አማራ ናቸው ማለት ነው (He descends from a culturally Oromo but a genetically Amhara population)፡፡ ስለዚህ አጼ ኃይለ ሥላሴ አማራ ብቻ ናቸው፡፡
ቢባል ቢባል እና አጼ ኃይለ ሥላሴ ኦሮሞ ደም አላቸው ብንል እንኳ ሊሆኑ የሚችሉት በአንድ አያታቸው ብቻ ነው ማለት ነው፡፡ ይህም ማለት 75% አማራ ናቸው ማለት ነው፡፡ በጀነቲክ ሳይንስ ደግሞ 25% is recessive while 75% is dominant gene. ይህ ማለት 25 ከመቶው ጅን በ75 ከመቶው የተሸፈነ ወይም ዋና ያልሆነ፤ የዘር ሀረግን በዋናነት ማስተላለፍ የማይችል፤ ለራሱ የተወሰነ ማለት ነው፡፡ አንድ ሰው 75 ከመቶው የወረሰበትን ወላጅ ዘር ሙሉ በሙሉ ይይዛል ማለት ነው፡፡ አንድ ሰው ግማሹ ወይም 50 ከመቶው አማራ ቢሆን እንኳ አማራ ነው እንኳን 75 ከመቶው! እንዳለመታደል ግን ለግማሽ ክፍለ ዘመን ከዘለቀው የኢ-አማራ ማድረግ ሂደት የተነሳ አማራን ኦሮሞ ለማድረግ 25 ከመቶ በቂ ነው፡፡ 75ን ለ25 በግድ እጁን ጠምዝዞ ማስረከብ! በእናንተ በራሳችሁ ክርክር እንኳ 75 ከመቶ የሆነን ሙሉ አማራ ለ25 ከመቶው አሳልፋችሁ ለመስጠት የምትንጦለጦሉ አማራ ተብየዎች ማፈር አለባችሁ፡፡ ያም አለ ይህ አጼ ኃይለ ሥላሴ ከፍ ዝቅ የሌለባቸው አማራ ናቸው፡፡ እዚህ ጋር የተጠቀሰው ጀነቲክ ማብራሪያ ነው፡፡ ከዚህ ውጭ ደግሞ ንጉሱ በባህል ሙሉ በሙሉ አማራ ናቸው፡፡ ማለትም አንድን ህዝብ ከዘሩ በተጨማሪ አማራ የሚያደርገው ሳይንሳዊ የባህል ማብራሪያ ነገሮችን ሙሉ በሙሉ፤ አንድም ሳያጓድሉ የያዙ ንጉስ ናቸው፡፡ ኧረ በበለጠ ሁኔታ፡፡
በነገራችን ላይ ካይማር እና አክናሁስ “አጼ ሀይለ ስላሴ በታሪክ ፊት ብላችሁ” ስለፓኪስታን ምናምን የምትዘባርቁትን ሀሜት አይቸዋለሁ፡፡ ያው ሀሜት ከሀሜትነቱ አይዘልም…ታውቃላችሁ ወይም ታውቃለህ፡፡ የፓኪስታኑ ጉዳይ አስጨንቆኝ ሳይሆን አንድ ምክር ለመለገስ ነው ያንን ትርኪ ምርኪ ሀሳባችሁን ያነሳሁት፡፡ ይህንን ሀሳብ የሚያራምዱትን ዋነኞቹን የጀርመን ፕሮፌሰሮች አውቃቸዋለሁ፡፡ እዛ ትግራይ አካባቢ ያስተምራሉ፤ ሪሰርች ይሰራሉ፡፡ ለአማራ ያላቸው ክፉ አመለካከት ግን ከአንድ የአድዋ ተወላጅ ወያኔ ቢብስ አንጅ አያንስም፡፡ አንዱ በተለይ ትግሬን ደግፎ እዚህች አገር ላይ ለደረሰው ችግር ሁሉ አማራን ተጠያቂ አድርጎ የሚከራከር ነው፡፡ ስለፓኪስታኑ ጉዳይ ሲያራግብ ማስረጃ አምጣ ስለው ንጉሰ ራሳቸው የጻፉት ጽሁፍ ላይ የሆነ ፎቶ አይቸ ምናምን ነው የሚለው፡፡ ሌላም የሚዘባርቀው ነገር አለ፡፡ ግን አላማው የወያኔን ጸረ አማራ ስራ ማገዝ ነው፡፡ ይህንን ስላችሁም ዝም ብየ አይደለም፡፡ የጀርመን ምሁራን ለኦነግ፤ ሻእብያና ወያኔ በትጥቅ ትግል ወቅት የፕሮፓጋዳ ድጋፍ ያደርጉ ነበር፡፡ አንድ ጊዜ ዘነበ ፈለቀ “ነበር” ብሎ በጻፈው መጽሀፍ ውስጥ ደርግ ሁለት የደህንነት ሰራተኞችን ወደምእራብ ጀርመን መላኩን፤ የደህንነቶችም ተልእኮ አንድ የሸማቂዎች ዋና ሰውን ለመግደል እንደነበረ፤ ነገር ግን አንደኛው ደህነነት ቦምቡን በመጽሀፍ መልክ ለማጥመድ እየሰራ በነበረበት ጊዜ ሌላኛው ደህንነት ውጭ ቆይቶ ድንገት ወደክፍላቸው ሲገባ ሳያስበው ቦምቡን ነክቶት መፈንዳቱን፤ ያንንም ተከትሎ ይህንን ከፍንዳታ የተረፈ ደህንነት የምእራብ ጀርመን የደህነነት ሰራተኛ አይኑን ደንቁሎ አውጠቶ ጥሎት ወደአዲስ አበባ መመለሱን እንደጻፈ ነገርኩት፡፡ ይህም ፕሮፌሰር “ደርግ የላካቸው እነዛ ደህንነቶች ማንን ለመግደል እንደነበር አውቃለሁ፤ ለተቃዋሚዎች የፕሮፓጋንዳ ድጋፍ ያደርግ የነበረን ጓደኛየን ለመግደል ነበር” ብሎ ነገረኝ፡፡ እና ምን ማለት ፈልጌ ነው፡- አጼ ኃይለ ሥላሴን ኢ-አማራ ማድረግ ወይም አማራ ላይ መዝመት የዚህ አገር አቀፍ ብቻ ሳይሆን አለማቀፍ ተልእኮም አካል ነው እያልኳችሁ ነው፡፡ ሀሜትን እንደማስረጃ በማቅረብ ወይም ማረጋገጥ የማትችሉትን ወሬ በማዛመት አማራነታችንን ከመጉዳት እንድትታቀቡ ለማሳሰብም እወዳለሁ፡፡
ከላይ በተጠቀሰው መልኩ እየተደረገ ያለው ነገስታቶቻችንን ኢ-አማራ ማድረግ ምን ጉዳት ያመጣል የሚለውን እንመልከት፡፡ አማራ የሆኑትን ነገስታቶቻችን አማራ አይደሉም ስንል ብዙ ነገር እናጣለን፡፡ ዋና ዋናዎቹም አምሐራ ነጻ ህዝብ ነው ስንል አማራ ከጥንት ጀምሮ እስከ ዘመነ ቅኝ ግዛት ድረስ በማንም ተገዝቶ አያውቅም ማለታችን ነው፡፡ በአለም ደረጃ ቅኝ ያልተገዛች ኢትዮጵያ ሲባል የዚህ ድል ዋናው ተዋናይ አማራ ነው፡፡ የማእከሉ ማእከል ላይ ደግሞ አማራ ነገስታት ይገኛሉ፡፡ አጼ ቴዎድሮስ አማራን በማሰባሰባቸው በኋላ የመጡትን ወራሪዎች በአንድነት እንዲመክት እድል አመቻቹ፡፡ ይህንን አጼ ቴዎድሮስ የሰበሰቡትን እና በሀይለኛ ክንድ ደቁሰው አንድ ያደረጉትን አማራ በመጠቀም ዳግማዊ ምኒልክ የበለጠ በማጠናከር የመከላከያ ወረዳቸውን አስፋፉበት፤ የተወሰደውንም መሬት መለሱበት፡፡ የመከላከያ ወረዳ ማስፋት ምን ማለት ነው? ንጉሱ የጥንት ግዛታቸውን ከማስመለስ ባለፈ ዙሪያቸውን በስፋት ከያዙበት ምክንያቶች አንዱ ቅኝ ገዥዎች ምናልባት ወደመሀል እንምጣ ቢሉ እዛው በረዥም ዳርቻ ለመከላከል በማሰብ እንደሆነ መገመት አይከብድም፡፡ ከጅቡቲ ወይም ሀርጌሳ ተነስቶ የሚመጣ ሀይል መሀል ኢትዮጵያ ወይ አማራ ላይ ከመድረሱ በፊት መከላከል ይቻላል፡፡ በጋምቤላም በሩዶልፎ (ደቡብ፡ ኬንያም) እንዲሁ ነው፡፡ ይህን የተስፋፋ የመከላከያ ወረዳ በመጠቀም እና ሰፊው ግዛት የፈጠረውን አቅም በመጠቀም በወራሪዎች ላይ አለም አቀፍ ድል ተጎናጸፉ፡፡ አጼ ኃይለ ሥላሴም በበኩላቸው ከዚህ ታላቅ ንጉስ የተረከቡትን አገር እና ነጻነት ለማስጠበቅ በነፍጥ ተፋልመዋል፡፡ አልሆን ሲልም ወደ ውጭ ሄደዋል፡፡
እዚህ ላይ ንጉሱ ወደውጭ መሄዳቸውን እንደሽሽት የሚቆጥሩ አሉ፡፡ ይህ ግን ውሀ የማያነሳ ክርክር ነው፡፡ አምባሳደር ብርሀኑ ድንቁ “ቄሳርና አብዮት” በተሰኘች መጽሀፉ ይህንን ነገር በሚገባ አብራርቶታል፡፡ ብርሀኑ ድንቄ ለመከራከሪያነት ያቀረባቸው ጭብጦች የአጼ ኃየለ ሥላሴን ከአገር መውጣት እና የአጼ ቴዎድሮስን መቅደላ ላይ መሰዋት ነው፡፡ እንደ ብርሀኑ ድንቄ አባባል ለአንድ አይዲያሊስቲክ ኢትዮጵያዊ አጼ ኃይለ ሥላሴ ማይጨው ላይ ራሳቸውን ማጥፋት ነበረባቸው፤ ራሳቸውን ቢያጠፉ ትክክል ናቸው፡፡ በሌላ ጎኑ ለአንድ ፕራግማቲክ ሰው አጼ ኃይለ ሥላሴ ሁኔታው እንደማይሆን ሲያውቁ አገር ለቀው መሰደዳቸው ተቀባይነት አለው፡፡ እዚህ ጋር ክርክሩ በአይዲያሊስት እና ፕራግማቲስት ተቃርኖዎች ላይ ነው፡፡ ማለትም አንድ አይዲያሊስት የአጼ ኃይለ ሥላሴን ድርጊት ኮንኖ ሊከራከር ይችላል፡፡ በሌላ ወገን አንድ ፕራግማቲስት ግን የንጉሱን ድርጊት ደግፎ ሊከራከር ይችላል፡፡
በአጭር አገላለጽ ምን ማለት ነው፡- ንጉሱ መሰደዳቸው ተጨባጭ ለውጥ አምጥቶአል፡፡ ንጉሱ እዛው ላይ ሞተው ቢሆን እና ጣልያን ተቆጣጥሮን ቢሆን ኖሮ የኢትዮጵያ ወይም የአማራ ነጻ ህዝብነት ወይም አምሐራነት አከተመ ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም ንጉሱ በመሰደዳቸው የኢትዮጵያ ስልጣነ መንግስት አብሮ ተሰደደ ማለት ነው፡፡ ያ ማለት የኢትዮጵያ መንግስት ከአገሩ ተሰዶ በሌላ አገር በስደተኝነት ቀጥሎ ነበር ማለት ነው፡፡ በሌላ አገላለጽ ንጉሱ አገራቸውን እንጅ ስልጣናቸውን አልተቀሙም፡፡ ዙፋናችንም አልተወገደም፡፡ ንጉሱ በስደት መንግስታቸውን ይዘው በመሰደዳቸው ኢትዮጵያ በጣልያን ስር ሆናም የመንግስትዋ ህልውና አላከተመም ነበር፡፡ ይህ በራሱ ትልቅ ጥቅም አምጥቷል፡፡ ንጉሱ በስደት ሆነው ዲፕሎማሲያዊ ትግል በማድረግ የአላይድ ፓወርስ ድጋፍ ማግኘት ችለዋል፡፡ ያም ድጋፍ በኋላ ከአርበኞች ትግል ጋር ተደማምሮ በስደት የነበረውን መንግስት ተመልሶ በቦታው እንዲተከል አድርጎታል፡፡ አገር ውስጥ ይደረግ የነበረው የአርበኝነት ትግልም ይህንን የንጉሱን ዲፕሎማሲያዊ ትግል ለማገዝ ረድቶአል፡፡ እዚህ ላይ የንጉሱን ዲፕሎማሲያዊ ትግልና ያም ትግል ያስገኘውን አለማቀፍ ድጋፍ ለማሳነስ ሲል አርበኞች ነጻ ሊያወጡን ይችሉ ነበር ብሎ ሊያስብ ይችላል፡፡ እኔ ግን የአርበኞች ትግል ብቻውን ነጻነታችንን ያጎናጽፈን ነበር ብየ ለማሰብ ይከብደኛል፡፡ በምንም መልኩ የአርበኞች ተጋድሎ ወደር የለሽ መሆኑ የታመነበት ነው፤ ይሁንና የንጉሱ ዲፕሎማሲያዊ ትግል የላቀውን ሚና ተጫውቷል ብየ አስባለሁ፡፡ ለምሳሌ Michela Wrong “I didn’t Do It For You” በተባለው መጽሀፏ ውስጥ የንጉሱ ቀኝ እጆች የነበሩት የሲልቪያ ፓንክረስት ቤተሰቦች በተለይም ሲልቪያ ፓንክረስት የነበራትን ተደማጭነት በመጠቀም በየአገሩ እየዞረች ለንጉሱ ድጋፍ ታሰባስብ ነበረች፡፡ የድጋፉም አይነት የዲፕሎማሲ እና የገንዘብ ነበር፡፡ በዚህም ብዙ እንግሊዛዊያንን እና ከዛም አልፎ ሌሎች አውሮፓዊያንን ከንጉሱ ጎን ማሰለፍ ችላለች፡፡ ግን ደርግ ንጉሱን ለማጥላላት ብዙ ሰርቷል፡፡ የዛም ክፉ ፕሮፓጋንዳ ቅሪት በወያኔ ህይወት ተዘርቶበት ወደራሳችን ወገኖችም ተጋብቶ እስከዛሬ ድረስ አለ፡፡
ስለዚህ የነገስታቶቻችን አማራነት ከጣልን አምሐራ ነጻ ህዝብ ነው የምንለውን አብረን መጣል አለብን፤ ኢትዮጵያ ወይም አማራ ቅኝ አልተገዙም የሚለውን መወርወር አለብን፤ የጥቁር ዘር አንጸባራቂ የሆነ አለማቀፍ ድል ሲያደርግ ዋነኛው ህዝብ አማራ እና መሪዎቹ አማራ ነገስታት መሆናቸውንም መጣል አለብን፤ እነደአማራነታችን የወረስነውን አኩሪ ገድል ሁሉ አብረን መጣል አለብን ማለት ነው፡፡ አንዱን የአማራነት አሻራ ስንጥል ሁሉንም እየጣልን እንደሆነ ማወቅ አለብን፡፡ በራሳችን ነገስታት ላይ ስንዘምት በራሳችን ላይ እየዘመትን መሆናችንን እንገንዘብ፡፡ አማራነታችንን ሌሎች የሚሸራርፉት እና የሚያጠፉት ይበቃል፡፡
መለክ ሐራ